#የሀሳብ_ዕቁብ_እንጣል
✍️ ብዙ ሰው ገንዘቡን ቆጥቦ ሕይወቱን ወደፊት ለማራመድ ሲል ከገቢው ቀንሶ፣ ከፍጆታው ቀምቶ እቁብ ይጥላል፡፡ ጥሩ ነው እቁብ መጣል፡፡ ብዙ ሰው ግን በገንዘቡ ዕቁብ አንደሚጥለው ሁሉ ማንነቱን ለማብሰል፣ ምንነቱን ለመረዳት፣ የሕይወት መንገዱን ለማደላደል፣ በራሱ ላይ ድልን ለመጎናፀፍ፣ የተሻለ ማንነት ያለው ሰው ለመሆን ሲል የሃሳብ ዕቁብ ሲጥል አይታይም፡፡
✍️ ሃሳብ እንደገንዘብ የችግር ጊዜ ደራሽ ነው፡፡ አብዛኛው ሰው ችግሩን ለመፍታት የሚሞክረው በገንዘቡ ብቻ ነው፡፡ ገንዘብ ኖሮ ችግርን የሚቋቋም ጠንካራ ሃሳብ ከሌለ ዋጋ የለውም፡፡ የበሰለ ሃሳብ ኖሮ ገንዘቡ ባይኖር ብዙም ችግሩ አይባባስም፡፡ ሃሳቡ ችግርን መሻገሪያ ገንዘብን መፍጠር ይችላልና፡፡ የበሠለ ሃሳብ ከጨለማ ሕይወት የሚያወጣ ድልድይ ነው፡፡ አሻጋሪና ተሻጋሪ ሃሳብ መፍጠር የሚቻለው ቀድመን በጣልነው የሃሳብ ዕቁብ ነው፡፡ የተከማቸ ሃሳብ ዕውቀትን ይገነባልና፡፡
✍️ ሰው ጤናማ ስሜት፣ የተረጋጋ ሕይወት፣ የበሠለ ማንነት፣ የሃሳብ ልዕልና እንዲኖረው ከዚህ በላይ ሃብት፣ ከዚህ በላይ የትምህርት ደረጃ፣ ከዚህ በላይ የስልጣን ሹመት፣ እንደዚህ ዓይነት ወዳጅና ቤተሰብ ሲኖረው ነው የሚል የተሠመረ ወይም የተቀመጠ መስመርም ሆነ ድምዳሜ የለም፡፡ ይሄን ሁሉ እውን እንዲሆን የሚያደርገው የሰው የገዛ ራሱ ሃሳብ ነው፡፡ ሃሳቡ ዕውቀት ሆኖ በተግባር ሲፈተን በየትኛውም ጊዜ ለሚደርስበት የኑሮ ውጣውረድ ችግሩን መፍቻ ቁልፍ ሆኖ ያገለግለዋል፡፡ ምክንያቱም ጤናማ ያልሆኑ ስሜቶችና የሕይወት ውሳኔዎች ጤናማ ካልሆነ ሃሳብና አመለካከት የሚመነጩ ናቸው፡፡
✍️ ጤናማ አስተሳሰብን መፍጠር የሚቻለው ደግሞ ሰው ከሃሳቦቹ ጋር መጨዋወት፣ መሟገት፣ አልፎ ተርፎም ሃሳቦቹን በዕውቀት ለውጦ የተፈተነ ማንነትን ሲቀዳጅ ነው፡፡ የተፈተነ ማንነት ለፈተና አይደነግጥም፡፡ ፈተናውን እንዴት እንደሚያልፍ እንጂ ፈተናው ለምን እኔ ጋር መጣ ብሎ በሆነ ባልሆነው ሲጨናነቅ ጊዜውን አይፈጅም፤ ራሱንም አይረብሽም፡፡
ስኮትላንዳዊው ፀሐፊ ሳሙኤል ስማይል ሲናገር፡-
‹‹ሃሳብን ዝራ፣ ተግባርን እጨድ፡፡ ተግባርን ዝራ ልማድን እጨድ፡፡ ልማድን ዝራ ባህርይን እጨድ፡፡ ባህሪህን ዝራ ፍፃሜን እጨድ!›› ይላል፡፡
✍️ እውነት ነው! ያልተዘራ ሃሳብ ተግባር ሆኖ አይበቅልም፤ የስራዎቹ ፍሬዎችም ደርሰው አይታጨዱም፡፡ ተግባር መልካም ልማድን የሚጠራው የተዘራው የሃሳብ ዘር ምርታማ ሲሆን ነው፡፡ ዘሩ ደግሞ ሃሳብ ነው፡፡ መልካም ልማድ ሠናይ ባህሪይ የሚሆነው ከሃሳቡ ጀምሮ ተግባሩም ያማረ ሲሆን ነው፡፡ ባህርይ ደግሞ አጨራረስን ያሳምራል፡፡
✍️ አዎ! ብዙዎቻችን ጅማሬአችን ጥሩ ሆኖ ሳለ ፍጻሜአችን የተበላሸ ይሆናል፡፡ አንዳንዶች ደግሞ ጅማሬአቸው ተስፋ የሚያስቆርጥ ሆኖ በመሃል ሃሳባቸውን አብስለው አጨራረሳቸውን ያሳምራሉ፡፡ የተሳካላቸው ደግሞ አጀማመሩንም አጨራረሱንም አንድ ያድርጋሉ፡፡ አባቶቻችን ማታዬን አሳምረው የሚሉት ለዚህም አይደል!
✍️ ፈላስፋው ዳዮጀኒስ አንድ ዘናጭ ሠው ያይና ጠጋ ብሎ ቢያወራው ዘናጩ ሠው ሃሳቡ የቆሸሸ ስለነበር እንዲህ አለው፡- ‹‹ይሄ ሠው ቤቱ ያምራል፤ ውስጡ ግን ግም ነው›› ብሎት ቁጭ አለ፡፡ የልብስ ንጽሕና በውሃ ይታጠባል፤ የአስተሳሰብ ቆሻሻን ለማፅዳት ግን ብዙ ጊዜን ይፈልጋል..! የፀዳ ሃሳብ የሚገኘው ልክ እንደማስቲካ ብዙ ሃሳቦችን አኝኮ የማይጠቅመውን ሲተፋው ነው፤ ልክ እንደ ከረሜላው ደግሞ መልካም አስተሳቦችን አጣጥሞ ሲውጥ ነው፡፡
ጠቢቡ ንጉስ ሰለሞን፡- ‹‹ሰው በልቡ እንዳሰበ እንደዚያው ነው (As the man thinks, so is he)›› ይላል፡፡
✍️ ሐቅ ነው! ሰው የሚያስበውን ነው፡፡ የሚያስበው ምንም ይሁን ተግባሩም ያው ነው የሚሆነው፡፡ ደጋግሞ የሚያደርገው ነገር ደጋግሞ የሚያስበውን ነው፡፡ ሰው ሃሳቡን ካሳመረ ተግባሩን ማሳመር ይችላል፡፡ ያማረ ተግባር የተዋበ ልምድን ያመጣል፡፡ ልምድ ባህሪይን ጠርቶ መጨረሻን የተሳካ ያደርጋል፡፡
✍️ ስለዚህ ሰው ሃሳቡን የተሻለ ለማድረግ ብዝሃ ሃሳብን መጎናፀፍ ይኖርበታል፡፡ የሃሳብ ዕቁብ እየጣለ የተከማቸ ሃሳብን ይይዛል፤ የበዛ ሃሳብ ያለው ለአስተሳሰብ ጥበት በሽታ አይጋለጥም፡፡ ሃሳቡን በራሱ መንገድ ብቻ ሳይሆንም በሌሎችም አስተሳሰብ ስለሚዋጀው ተግባሩም፣ ልምዱም፣ ባህሪውም፣ ማንነቱም ጥሩ ይሆናል፡፡
የሃሳብ ዕቁብ እየጣልን ብዘሃ ሃሳብን እናከማች!
Comments
Post a Comment